የኢትዮጵያ ሕክምና ማህበር 60ኛው ዓመታዊ የሕክምና ጉባኤና ዓለም አቀፍ የጤና አዉደ ርዕይ አስመልክቶ የተዘጋጀ ጋዜጣዊ መግለጫ

የኢትዮጵያ ሕክምና ማህበር ከተመሰረተ 1954ዓ.ም ጀምሮ በህክምና አገልግሎት አሰጣጥ ጥራት፣ በታካሚዎች ደህንነት እና በአጠቃላይ በህክምናው ዘርፍ ቁልፍ ሚና በመጫወት አገልግሎት እየሰጠ የሚገኝ ማህበር ነው፡፡

የማህበሩ ራዕይ ጥራት ያለው የጤና አገልግሎት ማግኘት የሚችል ጤናማና የበለፀገ ማህበረሰብ ማየት ነው፡፡ ይህንን እውን ለማድረግ ይረዳ ዘንድም ከሚመለከታቸው የመንግስት መስሪያ ቤቶች በተለይም የጤና ሚኒስትርን ጨምሮ የማህበረሰብ ክፍሎች እንዲሁም ከስፔሻሊቲ ሶሳይቲዎች እና ከማህበሩ አባላት ጋር በመሆን ምክክር የሚያደርግበት ዓመታዊ ጉባዔ ያካሂዳል፡፡

በዚሁ መሰረት ዘንድሮ 60ኛውን ዓመታዊ የሕክምና ጉባኤና ዓለም አቀፍ የጤና አዉደ ርእይ ከየካቲት 29 – 30/2016 ዓ.ም በኢትዮጵያ ስካይላይት ሆቴል ለማካሄድ ዝግጅቱን እያጠናቀቀ ነው፡፡ ጉባኤው በአካል በመገኘት ከሚሳታፉ አባላትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተጨማሪ የቀጥታ ስርጭት ሽፋን በተለያዩ የሚዲያ አማራጮች የሚሰጠው ይሆናል፡፡

በአመታዊ የህክምና ኮንፈረንሳችን (AMC) በሃገር ውስጥ እና በውጭ ሃገር የሚኖሩ እውቅ የህክምና ባለሙያዎች ያላቸውን እውቀት የምርምር ግኝቶችን እና የህክምና ልምዶችን ለመለዋወጥ የሚረዳ መድረክ ነው።በጉባዔው የዓመቱን መሪ ቃል መነሻ በማድረግ የፓናል ውይይቶች ይካሄዳሉ።

CEU የሚያስገኙ የሙያ ማሻሻያ ስልጠናዎች ይሰጣሉ፤ የሳይንሳዊ ግኝቶች የሚቀርቡበት ክፍለጊዜም ተዘጋጅቷል።

የኢትዮጵያ ሕክምና ማህበር 60ኛው ዓመታዊ የሕክምና ጉባኤና ዓለም አቀፍ የጤና አዉደ ርእይ ከ600 በላይ የተከበሩ የህክምና ባለሙያዎችን እና ከውሳኔ ሰጪዎች በተጨማሪ ከሁሉም ክልል የሚመጡ የማህበሩ አባላት ተወካዮች፣ከተለያዩ የጤና ባለሙያዎች ማህበራት እና ስፔሻሊስቶች ማህበራት የተውጣጡ ተወካዮች፣የህክምና ኮሌጅ ኃላፊዎች እና የመንግስት አካላት ጨምሮ የሚያሳትፍ ጉባዔ ሲሆን ዓለም አቀፍ የጤና አዉደርእይ ከ100 በላይ ድርጅቶች የሚሳተፉበት እንዲሁም ከ2,000 በላይ ሰዎችም ይጎበኙታል ተብሎ ይጠበቃል።

በተጨማሪም በየዓመቱ ተጠባቂው የኢትዮጵያ ሕክምና ማህበር የሽልማት መርሃግብርም በአራት ዘርፍ ሽልማት የሚሰጥ ይሆናል
• የኢትዮጵያ ሕክምና ማህበር የአመቱ ምርጥ የህክምና ተማሪዎች ሽልማት 2016
• የኢትዮጵያ ሕክምና ማህበር የሕይወት ዘመን ሽልማት 2016
• የኢትዮጵያ ሕክምና ማህበር ተፅዕኖ ፈጣሪ እና ምርጥ ወጣት ሀኪም ሽልማት 2016

• የኢትዮጵያ ሕክምና ማህበር የ2016 የአመቱ ምርጥ ተቋም

በአጠቃላይ ዝግጅቱ ለየት ባለመልኩ ለሁሉም ባለድርሻ አካላት እሴት እንዲጨምር እና ለሀገራችን የህክምና እድገት የራሱን ድርሻ በመወጣጥ ጥራት ያለው ሕክምና ማህበረሰባችን እንዲያግኝ ለማድረግ የሚያስችሉ ሳይንሳዊ ግኝቶች የሚቀርቡበትና የኢትዮጵያ ሕክምና ማህበር አባላት በየዓመቱ ተነፋፍቀው የሚገናኙበት በቀጣይ የማህበሩ ጉዞ ላይ ሚመክሩበትና አቅጣጫ የሚያስቀምጡበት ዓመታዊ የሕክምና ጉባኤ ነው፡፡